የኤጀንሲውን የመድኃኒት መዘርዝር በጥልቀት መከለሱ እንደ ሀገር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አለው ሲሉ የጤና ባለሙያዎች ተናገሩ
የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ በቀጣይ ሁለት አመታት በመላ ሀገራችን ለሚገኙ የመንግስት ጤና ተቋማት የሚያቀርባቸውን የመድኃኒት መዘርዝር በጥልቀት መከለሱ እንደ ሀገር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አለው ሲሉ ሀኪሞች ነሀሴ 26 ቀን 2012 ዓ.ም ተናገሩ፡፡
ዶ/ር መንግስቱ ሽፈራው በባህርዳር ፈለገ ሂወት ሆስፒታል ዩሮሎጅስት ሃኪም ሲሆኑ የመድኃኒት ክለሳው ከመጀመሪያው አንስቶ ሙያተኞችን ማሳተፉ መድኃኒቶች በሀኪሞች በኩል ለህብረተሰቡ የሚደርሱ በመሆናቸው ምን ምን አይነት መድኃኒት እንዲሚያስፈልግ መጠየቃችን እጅግ አስፈላጊ እና ግዴታም ነው ብለዋል፡፡
ሀገራችን ካላት የህዝብ ቁጥር እና የኢኮኖሚ እድገት አንጻር ሁሉንም አይነት መድኃኒቶች በመንግስት ገዝቶ ማቅረብ እንደማይቻል ገልጸው በጣም መሰረታዊ፡አንገብጋቢ እና ህይወት አድን በሆኑት ላይ መዘርዝሩ በማተኮሩ ቀድሞ ብዙ የማይፈለጉ የበሩት መድኃኒቶችን ያስቀራል ብለዋል፡፡
ቴክኖሎጅው የፈጠራቸው የህክምና ቁሳቁሶችንም ታሳቢ በማድረግ ለማህጸን፡አንጀት ካንሰር ታካሚዎች የሚረዳ ለስራችን አስፈላጊ የሆኑ ግብአቶች እንዲካተቱ አድርገናል ብለዋል፡፡
በየካቲት 12 ሜዲካል ኮሌጅ የህጻናት ሀኪም የሆኑት ዶ/ር መቅደስ ሽመክት በበኩላቸው በኤጀንሲው የመድኃኒት ግዥ መዘርዝር ውስጥ መካተት ያለባቸውንም ሆነ መውጣት ያለባቸውን ሙያዊ ትንታኔ በመስጠት ከነምክንያቱ ጭምር በመመካከር መግባባት ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡
አንድ አይነት መድኃኒት ሆነው በመጠናቸው ቢለያይም በ125፡ በ250 ወይም በ500 ሚሊ ግራም በሚዋጡ፡ በመርፌ ወይም ሹሮፕ መልክ ለሕጻናት፡ለአዋቂ ወይም ለጽኑ ህሙማን የሚሆኑትን የትኛው መልክ ቢወሰድ መልካም ነው ብለን ለይተናል ብለዋል፡፡በእብድ ውሻ ከተነከሱ በኋላ በታካሚዎች የሚወሰዱ መድኃኒቶች እንዲካተቱ አድርገናል ብለዋል፡፡
ዶ/ር ዮዲት ዳመነ የጥርስ ሃኪም ሲሆኑ ለስራቸው ማደንዘዥያ በተለያየ መልክ የሚያስፈልጋቸው ከመሆኑም በላይ በተለይ ለህጻናት ሲድከን የተባለውን በቅባት መልክ ያለው በስፕሬይ ወይም በጀል መልክ ቢቀርብ መልካም እንደሆነ አስተያየት ሰጥጠናል ብለዋል።
በመጨረሻም ሀሳባቸውን እንዲያጋሩን የጠየቅናቸው በአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የአጥንት ስፔሻሊስት የሆኑት ዶ/ር ሲሳይ በለጠ ከስራቸው ጋር የሚገናኙ መሳሪያዎች በተፈጥሯቸው ውድ በመሆናቸው በተመጣጣኝ እንዲቀርብ ለይተን አቅርበናል ብለዋል፡፡
በአወልሀሰን